Friday, May 1, 2009

የኅሊና ዕዳ :

የኅሊና ዕዳ :

መቼም ኅሊና የሚባል ነገር ካለ
ለቀናት መዘንጋት የሌለበት ያልተከፈለ ዕዳ አለ ::

እናት ለልጁ የሚሆነውን የሆነች
ተበድራ ተቀድማ ያስተማረች
እናታችን ኢትዮጵያ ...
ዛሬም በቀን ጎደሎ በጣዕር ተይዛለች ::

ያኔ የኔታ ቤት ተዘልቆ አቡጊዳ
አስኮላም ተገብቶ ሌላ ለማወቅ ስንሰናዳ
እሱም ሽው ብሎ አልቆ
የበረታውም ኮሌጅ ዘልቆ
ባለው ላይ ብዙ ጨምሮ
ተፈትሾ መተንተን መቻሉ ያወቀውን አብጠርጥሮ
ካባ ለብሶ ምሎ ሲሊውን ሊይዝ ...
ድንቁርናን ሊመታው አጠንክሮ

ያስተማረችንም በሌላት አቅሟ
እናታችንም ኢትዮጵያችን እማማ
ችግሯን አምቃ እንባዋን አደራርቃ
የደረሱላትን ልጆችዋን መርቃ
የሀዘን እንባዋ ደርቆ እንዳትኖር ትንሽ እንኳ ስቃ
እስከዛሬ እንደ ጂረት የፈሰሰው እንባ እንዳይበቃ
ዛሬም ኢትዮጵያችን አለች ቀን ጎሎባት ተይዛ በሀዘን ሲቃ
ምን ይብቃ ??!!

ያሁኑ ይባስ ! የፊጥኝ ተቀፍድዶ የታሰረ
እንዳይበላ ተፈርዶበት ተከንትሮ ያደረ
በቀን አንዴም አፉን ያልሻረ
እሱን እያየች ...
መኖር ከተባለ እናታችን ኢትዮጵያ ዛሬም አለች
በእንባ እየታጠበች ::

መቼም ኅሊና የሚባል ነገር ካለ
መዘንጋት የሌለበት ያልተከፈለ ዕዳ አለ ::

ካብራኳ የወጣ ጐፈሬ ዛሬ ጸጉሩን ተከርክሞ
አምሮበት ሺክ ብሎ በሱፍ ተሸልሞ
ከዘመኑ ሰዱቃውያን ጋር ገጥሞ
""በነፃ -ገበያ "" ቅኝት ይደለቃል እየመታ አታሞ
ሁሉ በእጁ ሁሉ በደጁ ...
ማን ከልካይ አለበት ይናገራል ደሞ

"" ኢትዮጵያማ አድጋለች
የነብስ -ወከፍ ገቢ በእጥፍ ጨምራለች ""

ህልቆ መሳፍርት የሌለውን
በየቤቱ በነብስ ወከፍ በራብ ሆዱ የሚጮኸውን
እንጀራ ቁም ነገር ሆኖ እሱን ያጣውን
ተመቸኝ ብሎ ""በአድጎአል "" ውሸት መጀቦን

ህሊና የሚባል ነገር ካለ
መዘንጋት የሌለበት ያልተከፈለ ዕዳ አለ ::

ያለ ነጋሪት ጋዜጣ
ይመስላል አዲስ አዋጂ የወጣ
እናታችን ኢትዮጵያ ታስራ ተቀፍድዳ
ታውጆባታል እንድትቀበር በሰዱቃዊ ቆዳ

ለወንበዴ አላጨበጭብም ያለው ቂም ተይዞበት
እሚበላው አሳጥተው በራብ አለንጋ ሲገርፉት
ያን ኩሩ ህዝብ ለዱቄት ሲያሰልፉት
ከዚህ በላይ ! አወረዱ እንጂ መዐት !

መቼም ኅሊና የሚባል ነገር ካለ
ያልተከፈለ ዕዳ አለ .....


ህዳር 20, 2001 ዓመተ ምህረት

No comments:

Post a Comment

Blog Archive