Thursday, March 28, 2013

እውነቱ ምንድነው?!

መንግስት ከአሶሳ አካባቢ እንዲፈናቀሉ የወሰነባቸው ኢትዮጵያውያን አካባቢውን ለቀው በመጓዝ ላይ እያሉ አስከፊ የመኪና አደጋ እንደደረሰባቸው፤ በአደጋውም ምክንያት 59 ሰዎች ህይወታቸው እንዳለፈ የኢሳት ዜና አገልግሎት መጀመሪያ  በማርች 26 በሰበር ዜናው ቀጥሎ ደሞ በተመሳሳይ ቀን የምሽቱ የዜና ስርጭቱ እንደዘገበ የሚታወስ ነው። ቦርከና ድሀረ-ገጽም ኢሳትን በምንጭነት ጠቅሶ ዜናውን አካፍሎ ነበር።  ህኖም ሃገር ቤት ካሉ “ነጻ” ጋዜጦችም ሆነ ከህወሓት/ኢህአዴግ ፈርጀ ብዙ የዜና ተቋማት በጉዳዮ ላይ ተጨማሪ ዘገባ ለማግኘት ተሞክሮ ነበር። በጉዳዮ ላይ በሃገር ቤት ሜዲያ ለሁለት ተከታታይ ቀናት የተዘገበ ነገር የለም። በይፋ በህወሓት/ኢህአዴግ ስር ያሉ የዜና ተቋማት በጉዳዮ ባይዘግቡ የሚገርም ነገር የለውም። ነገር ግን “በነጻ ጋዜጣ” ሂሳብ እንዲያዙ የሚፈልጉት ሌሎች የሃገር ቤት ጋዜጦች በጉዳዮ ላይ አለመዘገባቸው የሚያስነሳው ጥያቄ አለ። ከኢትዮጵያ ውጭ ያሉ ሌሎች የዜና ተቋማትም – እንደ የአሜሪካ ድምጽ የአማርኛ አገልግሎት እና የጀርመን ድምጽ ራዲዮ ጣቢያዎችም እንዲሁ በጉዳዮ ላይ አልዘገቡም።

በአንድ ሃገር ውስጥ በመኪና አደጋ 59 ሰው ሲሞት ትልቅ ዜና ነው፤ በዓለም ዓቀፍ ደረጃም ጭምር! ስሞኑን በህንድ የመኪና አደጋ ደርሶ ትልልቅ የሚባሉት የዓለም ዓቀም ሜዲያዎች ዘግበውታል። በደቡብ አፍሪካም እንዲሁ የመኪና አደጋ ደርሶ ሰፊ የዜና ሽፋን አግኝቶል። በሁለቱም አደጋዎች በተናጠል የጠፋው ህይወት ኢትዮጵያ ውስጥ ከትላንት ወዲያ ደረሰ በተባለው አደጋ ከጠፋው ህይወት ያነሰ ነው።  ስለዚህ ኢትዮጵያ ውስጥ ደረሰ የተባለውን አደጋ ዓለም ዓቀፍ የሚባሉት የዜና ተቋማት (እንደ ሮይተርስ ፣አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ፣አሶሴትድ ፕሬስ ያሉ) ፣ሃገር ቤት ያሉ ጋዜጦች እንዲሁም በኢትዮጵያ ቋንቋ የፕሮግራም ስርጭት ያላቸውን እንደ አሜሪካ ድምጽ ራዲዮ እና ጀርመን ድምጽ ራዲዮ ስለምን አልዘገቡበትም?! ለምን?!  አደጋው በአደጋነት ሂሳብ ብቻ የማይዘገብ እና ከዘር ማጽዳት ጉዳይ ጋር ስለሚነካካ ለመዘገብ አያስደፍርም የሚሉ ወገኖች አሉ። እንደሚባለው በዚህ አሳማኝ ሊባል በማይችል ምክንያት የ59 ሰው ህይወት ያለፈበትን አደጋ ሁኔታ እና የአደጋ መንስኤ ለሕዝብ አለማሳወቅ ከሜዲያ ፋይዳ እና ስነ-ምግባር አንጻር እንዴት ነው የሚታየው??

እንዲህ ያለ ጉዳይ ሲከሰት ኢፊሲያላዊ የሆነ መረጃ መገኘት የነበረበት ከፓሊስ ነበር። ያለው ተሞክሮ ግን ያንን አያመላክትም። ስሞኑን ሃገር ቤት – ያውም በመዲናዋ አዲስ አበባ -የሰው ህይወት ጠፋበት በተባለ ግጭት ላይ (የኮብልስቶኑን ያስታውሷል) ፖሊስ የማውቀው ነገር የለኝም እንዳለ ይታወሳል ፤ በሌሎች መስል ጉዳዮችም ላይ ፓሊስ መረጃ የለኝም የሚል መልስ የሚሰጥበት ተደጋጋሚ ሁኔታ አለ። 59ሰዎች ሞቱበት የተባለው አደጋ በትክክል ደርሶ ከሆነ ፤ በኢትዮጵያ ስም የሚነገድበት የህወሃት/ኢህአዴግ (“የኢትዮጵያ ዜና ድርጂት) ሰሞኑን የኢትዮጵያን ህዝብ በኢህአዴግ 9ኛ ጉባዔ እና የግድብ ወሬ እንዳፈነ አንድ እና ሁለት የለውም። ሌላ ጊዜ የጠፋ መርፌ የሚያገኙት የውጪ ሜዲያዎችም ጉዳዮ በትክክል ተከስቶ በዝምታ ማድበስበስ መርጠው ከሆነ ለአድሎአዊ አሰራራቸው ተጨማሪይ ማሳያ ይሆናል።

በሌላ አንጻር አደጋው ከናካቴው ያልተከሰተ ነገር ክሆነ ፤ ዘገባውን ለሕዝብ ያደረሰው ኢሳት በኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን የመረጃ አሰባሰቡ ስራ በብርቱ ሁኔታ መፈተሽ ይኖርበታል። ምን አልባት ሆነ ተብሎ የኢሳትን ገጽታ ለማጉደፍ ህወሓት/ኢህአዴግ በዘዴ ያደረገውም ነገር ሊሆን ይችላል። እውነቱ ምንድነው?!
________________________________
 በዚህ ብሎግ ላይ የሚወጡ ጽሁፎችን www.borkena.com ማግኘትም ይቻላል። ድህረ-ገጹ በተጨማሪም ወቅታዊ የሆኑ ዓለም ዓቀፍ እና የአፍሪካ ዜናዎችንም ያካፍላል።
 

2 comments:

  1. Dear Dimetros, you said it all it and it is my question too. very sad!!!

    ReplyDelete
  2. It looks like the accident has happened.The point is to get more supportive evidence.

    ReplyDelete

Blog Archive