Friday, October 2, 2009

ተስፋ የሚያስፈልገው ተስፋ አስቆራጭ በሚመስል ሁኔታ ነው

በትምህርት ቤቴ ቤተ መጽሐፍት ሰማይን ማየት በሚያስችለኝ
ቦታ ምቾት ባለው ወንበር ላይ ተቀምጫለሁ
የያዝኩትን ዳጎስ ያለ መጽሀፍ አነባለሁ
በተመስጦ ጉዳዪን እያኘኩ ገጾቹን ላፍ ላፍ አደርጋለሁ
አንዳንዴ ደሞ ንባቡን ትቼ እቆዝማለሁ
አይኔን ወደ ውጭ ልኬ ከምድር እስከ ሰማይ ማየት የቻልኩትን ነገር ሁሉ እማትራለሁ ::

አንዲት ነጭ ርግብ እየበረረች ተፋትልካ
ከመስታወቱ ተጋጭታ ለማጥመጃ የተቀመጠ የሚመስል የቆመ ሺቦ ላይ ብትሰካ
ልቤ በሀዘን ተነካ ::
ሁለቱም ክንፎቿ በሽቦው ተቸነከረ
የውስጧም ውሀ ፈሰሰ ወደታች ተንቆረቆረ
አንዱ እንደኔ ያያት መስታዎቱን ነካክቶ ለማስበረር ሞከረ ::

ልክ ሞቷን ለመጠባበቅ እንደመረጠች ነገር
እርግቧ አልቻለችም ትንሽ እንኳ ለመብረር መሞከር
ጸጥ አለች .
ግን ትተነፍሳለች ::
ልጁ ተስፋ ቆርጦ ተመለሰ
የኔም እጀ ወደ መጸሀፌ ተመለሰ ...ጠረጴዛውን ዳሰሰ
ንባቡን ብጀምርም እይታየ ትንሽ ደፈረሰ
ብዙ ደቂቃ ቢያልፍም አይኔ ከአንድ አንቀጽ አልፎ የትም አልደረሰ ::

ያኔ ንባቡን መልሼ አቆምኩ
እርግቧን እያየሁ መቆዘሜን ቀጥልኩ ::

እንዳንቀላፋች ናት
""ግን የታል የፈጠራት ?
እውነት ሁሉንም የፈጠረው እግዚያብሔር ነው ?"" እያልኩ
ከእግዜር ሙግት ጀመርኩ
ጥርጣሬየን አጠናከርኩ ::

"'ሰውስ እሺ ሀጢያት ይሰራል ይባል
አሁን ይቺ ርግብ ምን ይወጣታል
በእውነት ፈጥሯት ከሆነስ እንዴት ዝም ይላል
እንዴት ሞት ይፈረድባታል ??""
እያልኩ እንደሞተች ተስፋ በመቁረጥ
ግን ደሞ መሞቷንም በውል ለማረጋገጥ
መስታወቱን በጣቴ ብቆረቁር
እርግቧ ወደ ላይ ተነስታ መብረር
ወዲያው ደንግጨ ወይ እግዚያብሔር !!!
አፌ ተሳሰረ
ልቤም በጸጸት እና በእምነት ተሰበረ ::
በእኔ ብሶ በእግዚያብሄር ስላዘንኩ
እጂጉን ተጸጸትኩ
ማንበቡንም ትቼ ወደ ቤት ተመለስኩ
ያሳለፍኩትን የጥርጣሬ ዘመን በአእምሮየ ከለስኩ
አንድ ነገር አወኩ !
ለካስ ተስፋ የሚያስፈልገው
ተስፋ አስቆራጭ በሚመስል ሁኔታ ነው :
ተስፋም እግዚያብሔር ነው ::

በፈረንጆቹ በዲሴምበር ወር 2007 ላይ ትምህርት ቤት ያጋጠመኝ ነው ::

ቶሮንቶ
ተጻፈ ዛሬ ሐምሌ 12, 2001 ዓ .ም

No comments:

Post a Comment

Blog Archive