Monday, February 28, 2011

የዳቦ ወይስ የፖለቲካ ጥያቄ?

ድሮ ኮተቤ ኮሌጅ ስማር የረሀብ አድማ ተደርጎ ነበር:: በጊዜው የነበሩት የተማሪዎች መማክርት አባላት የህዋሀት አባልና አንዳንዶቹም ታጋይ የነበሩ ናቸው:: በደንብ አስታውሳለሁ እነዚህ አመራሮች የተሰበሰበውን ተማሪ የተጀመረው አድማ መቶ በመቶ ከምግብ አቅርቦት ጥራት ጋር የተያያዘ እንደሆነ እና የፖለቲካ ጥያቄ እንዳልሆነ አጽኖት ሰጥተው ""ፖለቲካ ከተነሳ በየለሁበትም""አይነት መንፈስ ተማሪውን ያስጠነቅቁ ነበር:: ከዚያም መፈክር ይጻፍ ተብሎ በአራት ቋንቋ ተጻፈ:: የማስታውሳቸው ""ረሀብ ጊዜ አይህብን"" ""ጋፊን ኬኛ ጋፊ እኛታቲ"" ""ጥያቄያችን የዳቦ ነው"" እና ""we demand bread"" ነበሩበት:: እውነት ለመናገር የዳቦ ችግር አልነበረም:: በእኛ ሀገር ስታንዳርድም ይቀርብልን የነበረው ምግብ አድማ የሚያስመታ አልነበረም:: እርግጥ ነው የካምፓስ ምግብ የጣዕም ችግር አለበት:: እሱ ደሞ ሀገራችን ደሀ እንደመሆኗ አድማ የሚያስመታ ጉዳይ አልነበረም:: በኍላ ሲገባኝ የምግብ ጥራት እና ""ጥያቄያችን የዳቦ ነው"" ጩኽት ትክክለኛ ምክንያት አልነበረም:: ጥያቄያቺን ""የፖለቲካ አይደለም"" የሚለውም ሀሳብ እንደዚያው::
ለአድማ ያነሳሳው ትክክለኛ ጉዳይ የታፈነ የማህበራዊ እና የፖለቲካ ችግር ነበር::

በ1992 ዓመተ ምህረትም አገሪቱን ሊያነቃንቅ የሞከረ የተማሪዎች አመጽ ተከስቶ ነበር:: የህዋሀት መንግስት ከ40 በላይ ንጹሀን ዜጎችን ገድሎበታል:: የዚህኛውም አመጽ ጥያቄ እንዲሁ ዙሪያ ጥምጥም ነበር:: ""የአካዳሚክ ነጻነት"" ጥያቄ ነበር በዋነኛነት የተስተጋባው:: ወያኔም እንደለመደው ያለ እፍረት ""ጥያቄው የአካዳሚክ ጥያቄ አይደለም:: የፖለቲካ ለውጥ ሊያመጡ የፈለጉ ኃይሎች ናቸው ያንቀሳቀሱት"" የሚል አስተሳሰብ ይዞ ተማሪውን የዘር ፖለቲካ በማራገብ ሊከፋፍለው ሞከረ:: ምናልባት ብዙዎቹ የፌስ ቡክ ጓደኞቼ የዚያ እንቅስቃሴ ቀጥተኛ ተሳታፊ የነበሩ በመሆናቸው ከላይ ያልኩትን ነገር እንደሚያስታውሱት እገምታለሁ::

ታዲያ ዛሬም ድረስ የማይገባኝ ነገር የአንድ ሀገር የዪኒቨርሲቲ ተማሪዎች ; በመሰረተ ሀሳብ ደረጃ የሀገሪቱ የወደፊት ተስፋ እና ሀገር ተረካቢ እንደመሆናቸው መጠን ቀጥተኛ የሆነ የፖለቲካ ጥያቄ መጠየቅ የማይፈቀድላቸው ለምንድን ነው?? እንደ ዜጋ የፖለቲካ መብት የላቸውም ወይ??

የኮተቤው የተማሪዎች እንቅስቃሴ ሲደረግ ወያኔ በጎጃም ገበሬዎች ላይ ይሄ ነው የማይባል ከፍተኛ በደል አድርሶባቸው ስሞታ ለማሰማት አዲስባ ድረስ የመጡበት ሁኔታ ነበር:: ተማሪው በገበሬው ላይ በተደረገው ነገር ተቃውሞን እና ሀሳቡን እንኳን እንዲገልጽ አልተፈቀደለትም ነበር:: ለምን? "" የፖለቲካ ጥያቄ"" ስለሆነ::

በተመሳሳይ ሁኔታ የ1992ም የአዲስ አበባ ዪኒቨርስቲ ተማሪዎች ""የአካዳሚክ ነጻነት"" እንቅስቃሴ ከመደረጉ ትንሽ ቀደም ብሎ ወያኔ በአብዛኛው የሀገሪቱ ክፍል በተለይም በኦሮሚያም በዜጎች ላይ ሽብር ይነዛ ነበር:: ዜጎች የኦነግ አባል ናችሁ እየተባሉ ቁም ስቅል ያዮ የነበረበት ጊዜ ነበረ:: ከኦሮሚያ አካባቢ የመጡ ተማሪዎች ተቃውሟቸውን ለማሰማት እንዴ በዮኒቨርሲቲው ጊቢ እስቅስቃሴ ሲያደርጉ የአጋዚ ሰራዊት በጨለማ ገብቶ የህዋሀት አባል ተማሪዎች መሪ ሆነው የተማሪ ወታወቂያ እየታየ ተማሪዎች ወደ እስር ተግዘዋል:: እንዲህ እንዲህ አይነት ወያኔ የሚወስዳቸው የፖለቲካ አካሄዶች ያለጥርጥር በወያኔ ፖለቲካ ላይ ጥያቄ ያስነሳሉ:: በሌላ በኩል የዮኒቨርስቲ ተማሪዎች የፖለቲካ ጥያቄ እንዲጠይቁ አይፈቀድላቸውም:: ""ጥያቄያችን የዳቦ ነው"" እየተባለ እስከመቼ ነው የሚኖረው?? የነገ ተስፋችን በማን እጂ ነው ያለው??


ሰሞኑን የግብጽ እና የቱኒዚያ ወጣቶች አብዮት አካሔዱ ብሎ የወያኔ መንግስት ሺብር ስለገባው ; ወላጆችን ሰብስቦ ልጆቻችሁን ያዙ እንዳለ ሰምተናል:: ሚገርመው ወላጆች ልጆቻቸውን የሚይዙት እኮ የፖለቲካ ጥያቄ እንዳያነሱ ነው:: በሌላ በኩል ይሄው መንግስት የኢትዮጵያ ወጣቶችን በተለያየ መልኩ እያደነዘዘ የፖለቲካ ድንፈፍ ሊያደርጋቸው እየሞከረ ነው::ቅጥ ያጣ ነቀት ማለት ይሄ ነው:: በወያኔ መንግስት ላይ ወጣቶች ሊያነሷቸው የሚገቡ ብዙ ጥያቄዎች አሉ::

እኔ ግን በዋነኛነት የምጠይቀው የህወሀት መንግስት የኢትዮጵያን ወጣቶች በስራ እድል እና በጥቅማጥቅም በመያዝ ታማኝ የስርዓቱ ተገዢዎች እንዲሆኑ የወሰደው እርምጃ ነው:: ኢትዮጵያውያን ዜጎች የትምህርት ደረጃቸው በሚፈቅድላቸው መጠን የመንግስት የስራ ዕድል የማግኘት መብት አላቸው:: ይህንን ህጋዊ መብታቸውን ዘንግተው ለስራ እድል ተብሎ የፖለቲካ እምነታቸውን መቸርቸር እና የማያምኑበትን የፖለቲካ እሳቤ እንዲያራምዱ መደረግ የለባቸውም:: የህዋሀት መንግስት በጉልበት እያስተዳደረው ባለው የኢትዮጵያ ሀብት የፖለቲካ መነገጃ የስራ ዕድል መፍጠሩ በኢትዮጵያውያን ወጣቶች እንደውለታ መታየት የለበትም :!: ህዋሀት ከኪሱ የከፈለበት ጉዳይ የለም:: እንደውም ባለፈው ከአቶ ስብሀት ነጋ በቪኦኤ እንደሰማነው ህዋሀት የትየለሌ የሆነ ሀብት እንዳጋበሰ ነው:: ያ ተረስቶ ጭራሽ ለኢትዮጵያውያን ውለታ እንዳደረገ ማሰብ ምን ያህል የፖለቲካ ድንዝዝነት እንደነገሰ ብቻ ነው የሚያሳየው::

እስከዛሬ ድረስ ቀጥተኛ የሆነ የፖለቲካ ጥያቄ ባለመጠየቅ ; የህዋሀት መንግስት የሀገሪቱን ሀብት እና ንብረት እንደፈለገው ሲያደርገው በመቆየቱ ህዋሀት የኢትዮጵያውያን ወጣቶች ውለታ አለበት:: ከገባው:: ህዋሀት ከስልጣን ከወረደ የተገኘው የስራ ዕድል ይጠፋል ብሎ ማሰብ የፖለቲካ ሞኝነትም ነው:: የኢትዮጵያ ወጣት ተስፋ ነገውን በእጁ በማስገባት እና ባለማስገባት ላይ የተመሰረተ ነው:: በህዋህት የፖለቲካ ዳረጎት አይደለም!! ህዋሀት ከስልጣን ቢሽቀነጠር ቀን የሚጭልምበት ኢትዮጵያዊ አይኖርም:: ከጨለመ የሚጭልመው ለራሱ ለህዋህት ብቻ ነው:: የፖለቲካ ለውጥ ደሞ ያስፈልጋል::ሀያ አመት ሙሉ የዘር ነጋሪት እየመታ ""በብሄር ብሄረሰቦች"" የማደናገሪያ ስልት የፖለቲካ ስልጣን በማያፈናፍን ሁኔታ ይዞ ሲዘርፍ ከኖረ የፖለቲካ ቡድን ነጻ መውጣት በራሱ ትልቅ ስኬት ነው:: ነጻነት የሌለው ወጣት ተስፋ አለኝ ሊል አይችልም! የደስታ ሆነ የስኬት; የተስፋ መሰረቱ ነጻነት ነው:: ነጻነት የሌለው ሕብረተስብ የትም ሊደርስ አይችልም::

Tuesday, February 15, 2011

ወይ ቫለንታይን?!

ሰው የመሆን ትርጉም የሚያጎላው ማሰብ እና ማገናዘብ መቻል ነው:: ከሌላው ፍጥረት የምንለይበትም ምክንያትም ይሄው ነው:: የሚያስብ እና የሚያገናዝብ ሰው ደሞ እንዳረጉት አይሆነም:: ይጠይቃል:: ""ለምን?"" ይላል:: ባለፈው በዚሁ በፌስ ብክ ፔጄ ላይ "" ዘመን የሰጠን እና የወሰደብን ነገር ምንድን ነው?"" የሚል የመወያያ ርዕስ አንስቼ የፌስ ቡክ ጓደኞች የጠበኩትን ያህል መልስ አልሰጡበትም:: እንደውም ምንም አልመለሱም:: የግብጽ ወጣቶች ሰሞኑን ትንግርት አሳይተውናል:: ዘመናዊነት የሰጣቸውን የቴክኖሎጂ ጥበብ -ኢንተርኔትን ተጠቅመው - አገሬን እወዳለሁ ይል የነበረ መሪያቸው ( ሙባረክ) የወሰደባቸውን ነጻነት በጽናት ታግለው አስመልሰውታል:: ሙባረክ የወሰደባቸውንም የትየለሌ ገንዝብ ለማስመለስ በዝግጂት ላይ ናቸው:: የተለያዩ የህብረተስብ ክፍሎች የሚገባቸውን መብት እንዲያገኙም ትግላቸውን ቀጥለዋል:: የግብጽ የለውጥ አብዮት አልቆአል ማለት አይደለም:: ከሁኔታቸው እንደተረዳሁት ትግሉን እዚህ ቦታ ላይ በቁሙ የሚጥሉትም አይመስለኝም:: እንዳልሆነ ሆኖ ሊሰበር ስለሚችል:: የግብጽ ወጣቶች የነጻነት ትግል መንፈስ ግን መንፈሳዊ ቅናት ያሳድራል:: የግብጽ ወጣቶች በዘመናቸው ላይ ተጽዕኖ ለማድረግ ሞክረዋል:: ዘመን እስከመጨረሻው ባሪያ እንዲያደርጋቸው አልፈቀዱለትም:: የግብጽ ወጣቶች ይሄንን ሁሉ ሲያደርጉ ኢትዮጵያ ውስጥ የቫለንታይንን ቀን ለማክበር በሬዲዮ እና በቴሌቭዥን ነጋሪት ይጎሰም ነበር አሉ:: አዲስ ነገር ኦንላይን ላይ ስለ ቫለንታይን ቀን የተጻፈውን አንብቤ በጣም ተገርሜአለሁ::
ወጣቱ እንደዚህ እንደዚህ አይነት -ከልብ ሆነው ሲያስቡአቸው ትርጉም የማይሰጡን አውሮፖዊ አስተሳሰቦች እና ባህሎች የሙጥኝ እያለ በያዘ ቁጥር; ትርጉም ያላቸውን እንደ ነጻነት ያሉ እና የሀገር ጉዳዮችን ቸል እያለ እና ከናካቴውም እየረሳ ይመጣል:: በመርህ ደረጃ ስናየው ፍቅር የበለጸጉ ሀገሮች ያወጡት ኮንቬንሺናል ቀን ያስፈልገዋል ወይ የሚለው ራሱ አንድ ጥያቄ ነው:: በባህልም በእምነትም እንደማውቀው ፍቅር የዕለት ተዕለት ጉዳይ ነው:: ያለፍቅር አይዋልም አይታደርም:: በተለይ እንደ ኢትዮጵያ ባለ ማህበረሰብ ውስጥ:: እርግጥ ነው ስጦታ ፍቅርን ይገልጽ ይሆናል:: ሀዲስ አለማየሁም ""ለሚወዱት ሰው የሚደረግ ስጦታ ከሚቀበለው ሰው ይልቅ የሚሰጠውን ሰው ልብ የበለጠ ያስደስታል"" ብለው ጽፈዋል:: ያስማማል:: ጥያቄው ግን የፍቅር መግለጫ ስጦታ ለመለዋለጥ እና ፍቅርን ለመግለጽ February 14 አይዲያል ነው ያለው ማን ነው? የቫለንታይንን ቀን myth የፈጠረው ማን ነው? ዓላማውስ ምንድን ነው ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል:: ስፔሻል የሆነ ቀን ከሆነ የሚፈለገው ""በኮንቬንሽን ደረጃ የሚከበርን ቀን የወል ይሆን እንደሁ እንጂ የግል ሊሆን አይችልም::
ከተጨባጭነት ስናየው ደሞ አውሮፖዎቹ እና አሜሪካዎቹ (ሌሎችም የበለጽጉ የእስያ ሀገሮች) የቫለንታይንን ቀን ቢያከብሩም የኢኮኖሚ ሁኔታቸው ይፈቅድላቸውል:: ጦሙን የሚያድር እና ስራ አጥ ማህበረሰብ በበዛበት ምድር ከአውሮፓዎቹ እና ከሌሎች ከሞላላቸው ሀገሮች እኩል የምናብ ቫለንታይንን የሚከበርበት ምክንያቱ ሊገባኝ አልቻለም:: ከላይ የጠቀስኳቸው ማህበረሰቦች ወጣቶች በተወሰነ መልኩ ምርታማ ናቸው:: ከዚያም ባለፈ የት ገባችሁ የት ወጣችሁ ምን አሰባችሁ የሚላቸው ጉልበተኛ መንግስት የለባቸውም:: የመንቃት እና ያለመንቃት ዕድሉ ያለው በእጃቸው ነው:: እኛ ጋር ያለው ነባራዊ ሁኔታ ሌላ:: ባለፈው ሳምንት ሀገር ቤት ስልክ ደውየ የማልጠብቀው የቅርብ ሰው ""የወያኔነት"" ፎርም ሞላሁ አለኝ:: ለምን እንደዛ ሆነ ብየ ስጠይቅ በቃ እንደዛ ካልሆነ ተምሮ ስራ ማግኘት አልተቻለም የሚል መልስ ነው ያገኘሁት:: የአንድ ሀገር ወጣት በዜግነቱ እና በችሎታው የስራ ዕድል ለማግኘት የማይችልበት ዘመን ላይ ተደርሷል ማለት ነው:: ግፈኛ የሚባለውን የደርግ አገዛዝ በደንብ አድርጌ አስታውሰዋለሁ ስዎች ስራ ለመያዝ የደርግ ፓለቲካ ደጋፊ መሆን እንዳለባቸው አላስታውስም:: አሁን ያለው መንግስት ግን በግልጽ ስራ አጥነትን ራሱ አስፋፍቶ ; የስራ ዐድልን ደሞ የፓለቲካ መነገጃ አደረገው:: የደርግ መንግስት ደሀ ነበረ:: የመንግስት ድርጂቶች እንደነበሩ አስታውሳለሁ:: ንብረትነቱ የደርግ ፖርቲ የሆነ የንግድ ተቋም እንደነበረ ግን አላስታውስም:: አንድ ጊዜ አቶ ስብሀት ነጋ የሚባሉት የህዋሀት ሰው በአሜሪካ ድምጽ የአማርኛ አገልግሎት ላይ እንደተናገሩት የህዋህት ፓርቲ እጂግ በጣም ሀብታም ነው ; መገመትም ያስቸግራል ነው ያሉት:: ይሄ ሁሉ ሀብት የተገኘው ደሞ በዛች በደሀ ሀገር ስም እና ከዛች ከደሀ ሀገርም ነው:: ስራ አጥነት ግን ተንሰራፍቷል:: ኢትዮጵያን የሚመራው የወያኔ/ህዋሀት መንግስት ደሞ ዜጎች ስራ ለማግኘት እንደ ዜጋ እንደ ኢትዮጵያዊ ሳይሆን ; የህዋሀት እና እህት ድርጂቶች ፓርቲ አባል መሆን እንደሚጠበቅባቸው እየነገረ ስራ ሲሰጥ ; ወጣቱ ህዋሀት/ኢሀዴግን እንደባለውለታ ሁሉ ያይ ጀመር አሉ:: ሚያሳዝነው ረሀቡንም ስራ አጥነቱንም የፈጠረው ( ቢያንስ ያስፋፋው) ሀዋሀት/ኢሀዴግ ሆኖ ሳለ; ይሔው ፖርቲ በፖለቲካ ወገንተኝነት መመዘኛ የስራ ሰጪ ሲሆን በጎ አድራጊ መንግስት ሁሉ ሆኖ ቁጭ አለ:: እንዳረጉት መሆን ማለት ይሄ ነው:: ይሄንን ለማሰብ ያልቻን ወይ ያልፈለግን ደርሰን ከሞላላቸው እኩል ""ቫለንታይን" ላይ ስንጠላጠል የሚገም ነገር ነው::

ዛሬ የቫለንታይንን ቀን ምክንያት አድርጌ አነሳሁት እንጂ የፈረንጆች አዲስ ዓመት ሲከበር አዲስ አበባ ሻራተን ጠጠር መጣያ እስከሚጠፋ ሰው ሞልቶ አበሻው የፈረንጆችን በዓል ቁጥር እይቆጠረ አክብሯል:: ""የኢትዮጵያ ቴሌቭዢንም"" ስርጭቱን በቀጥታ አስተላልፏል:: የምናስብ ትውልዶች ነን ለማለት ማስረጃ ማግኘት ሁሉ እየከበደኝ ነው:: ያ ሁሉ ነገር ሻራተን አዲስ ቢቀርም ኖሮ እኮ አንድ ነገር ነበር:: ሌላኛው ያልገባው ወጣት እንዲጓጓለት ተደርጎ በቀጥታ በቴሌቭዥን መተላለፉ ነው የሚያስቆጨው:: በየገጠሩ እና በክፍለ ሀገር ከተሞች ያለው ወጣት ያንን እያየ ኢትዮጵያ "አድጋለች"" እያለ እንዲሳሳት እና ማንነቱ እንዲወናበድበት እየተደረገ ነው ያለው:: ከታች ያለውን ክሊፕ ተመልከቱ::

http://www.youtube.com/watch?v=VceDMjlfLdQ

የኢትዮጵያውይንም ገና እየተረሳ "' x-mass'" ላይ ትኩረት እየተሰጠ እንደመጣ ነው የሚሰማው:: ትውልዳችንን እንዳረጉት እየሆነ ነው:: የሚያደርጉት ደሞ ራሱን ሳይሆን ሌላ አይነት::እየሆነ ያለውን ነገር ሁሉ ዝም ብለን በዘመን ተጽዕኖ ሂሳብ መያዝ አለብን? ነው ጠንከር ያለ ነገር አለ?? ማነው እየመራን ያለው? ወዴት ነው እየተመራን ያለነው? አሁን የተያዘው አካሄድስ ያስፈልገናል ወይ? የኢትዮጵያ ባህል አደንዛዥ ነው ጎታች ነው ...ምናምን ምናምን እየተባለ ሌላ አንደንዛዥ የሰው ሀገር ባህል እና አስተሳሰብ ያስፈልገናል ወይ? በእርግጥ የህይወት ትርጉሙ ምንድን ነው? ማንስ ነው የሚተረጉምልን? የደስታ ምንጩ ምንድን ነው?

በዚህ ጉዳይ ላይ ሀሳብ ብንለዋወጥ በጣም ደስ ይለኛል ::

Thursday, February 3, 2011

"I blow out first ..."

This evening I happened to listen to a conversation between two teenage boys in men's locker room in a gym. I will refer to them as B1 and B2.

B1: listen I've a question. My girl friend blow out a lot. Do you argue with your girlfriend very often?
B2: We do.
B1: like on big...big issues?
B2: We even argue on every little issues
B1: Who blows out first?
B2: depends. If I didn't eat I blow out first. lol

Blog Archive